የመጽሐፉ ርእስ፦ እጅ የበዛበት የኦሮሞ ፖለቲካ እና ኢትዮጵያዊነት
ጸሓፊ :- ዮሴፍ ከተማ ሆርዶፋ
የኅትመት ዘመን፦ ፳፻፲፫ ዓ.ም.
የገጽ ብዛት:- ፪፻፺፫
የሽፋን ዋጋ፦ ፻፴፭ ብር
እጅግ ሰውኛ በኾነ የልጅነት አሳዛኝ ገጠመኙ መጽሐፉን ይጀምርልናል:: በአደገባት ግንደ በረት ወረዳ፣ ካቺሲ ከተማ ውስጥ የእርሱ ዘመን አፍቃሬ ኦነግ ወጣቶች ያደረጉት ፀረ-መንግሥት ዐመፅ ኪሮስ የተባለ መምህርን ቤተሰብ በማጥቃት ሲደመደም በልጅነት ሥነ ልቦናው ላይ የፈጠረበትን ጫና ያሳየናል። ዐመፁ የብሔር ተኮር ጥቃት ገጽታ ሲይዝ አራስ የነበረችውን የመምህሩን ሚስት የኦሮሞ እናቶች ከልጆቻቸው ቁጣ መታደጋቸውን በእማኝነት ይተርክልናል።
ጸሐፊው ዲ. ዮሴፍ ከተማ በ0መፁ ወደ ዓመድነት ከተቀየረው ከመምህር ኪሮስ ቤት ፍርስራሽ ውስጥ አንዲት ደብተር ፈልጎ ያገኛል። የዕቃ ዕቃ ጨዋታ ሚስቱ ኾና ትሞሽር የነበረችው የመምህር ኪሮስ ልጅ የሳባ ደብተር ነበረች። ከዛ በኋላ የልጅነት ነፍሱ በጥያቄ ስትዋከብ እናገኛታለን።
ክስተቱን ሲገመግም፣ ጉድለቱን ነቅሶ ሲያወጣ፣ በአጠቃላይ እርሱ "የኦሮሞነቴ ፖለቲካ" እያለ የሚጠራውን የዘውግ ፖለቲካን በነጻ አእምሮ ሲታዘበው፣ ሲፈትሸው ሳየው የነፍሱ ቁንጅና ታየኝ።
በመጽሐፉ የኦሮሞ ፖለቲካ በስሑት ፍኖት ላይ እንዲገኝ ኢትዮዽያን ማፍረስ የሚፈልጉ አካላትን አጀንዳ በተሸከሙ ልኂቃን፣ በውጭ ጸሐፍት የተዛባ ታሪካዊ ዘገባ፣ የጨቋኝና ተጨቋኝ ትርክት በሚቀነቀንበት የሶሻሊዝም እጅ እየታመሰ መኾኑን ያሳየናል:: በዚህም ምክንያት ኢትዮጵያን እንደ ሀገር በመሥራት ወሳኝ ሚና ካላቸው ሕዝቦች አንዱ የኾነው የኦሮሞ ሕዝብ እውነተኛ ሐሳቦችን የሚያደምጥ የፖለቲካ ምሕዳር መጥፋቱን በመረጃ ያመላክታል።
ጸሐፊው በኦሮሚፋ "ሳብ-ቦና" (ኩሩ ብሔር) የሚል ጽንሰ ሐሳብ መኖሩንና ጽንሰ ሐሳቡም በቅኝ ግዛት ቀንበር ካለመገዛት ሥነ ልቡና የመጣ እንደኾነ ይነግረናል(ገጽ 13-14)። ይህ ነጻ ሕዝብ በ21ኛው ክ/ዘመንም ነጻ አውጭ አያስፈልገውም፤ ካስፈለገውም በግዝፈቱ ልክ እንደይገለጽ ከቀፈደዱት የጽንፈኝነት ፖለቲካ ነጋዴዎች ነው ነጻ መውጣት ያለበት በማለት ጠንካራ አቋሙን ያስቀምጣል።
በዚህ የሥነ ልቦና ውቅር ላይ የነበረው የኦሮሞ ሕዝብ ፖለቲካ በተንኮል የሮሮ ፖለቲካ ውስጥ እንዲዘፈቅ መደረጉን በቁጭት ያነሣል። ይህንንም የኦሮሞ ሕዝብ ባለፈበት የታሪክ ሒደት በተመሳሳይ ኹኔታ ያለፈን ሌላ ሕዝብ ታሪክ እያነፃፀረ ያቀርብልናል:: የመገንጠል ሓሳብ ይዘው ታገልን ያሉት ልኂቃኑ ትውልዱ ራሱን አናሳ አድርጎ እንዲመለከት ወደ ስሑት መንገድ ገፍተውታል። ይህን የጸሐፊውን ሓሳብ ደግሞ የስሑት መንገዱ ቀያሾች ከነበሩት አንዱ ሌንጮ ለታ ለጋዜጠኛና ጸሐፌ ተውኔት ቴዎድሮስ ተክለ አረጋይ በጸጸት መልክ ነግረውት፣ ከዚህ መጽሐፍ ጋር በተመሳሳይ ወርና ዓመት በታተመውና ፍልስምና ፮ በተሰኘ መጽሐፉ አስቀምጦልናል።
የዚህ መጽሐፍ ዋና ዓላማም:-
👉 ለሀገራዊ አንድነት የሚበጁ ነገር ግን ያልተደመጡ የኦሮሞ ሕዝብ ሐሳቦች እንዲደመጡ ማድረግ። ይኽም ፖለቲካው በትክክለኛ፣ አዎንታዊ በኾነውና የኦሮሞ ሕዝብ ይበልጥ በሚጠቀምበት መንገድ እንዲጓዝ ማድረግ መኾኑን ደጋግሞ ይነግረናል። (ገጽ 12 ፣ 17፣ 154 ፣ 185) ከቤተ መንግሥት እስከ ቤተ ክህነት የነገሡ ሐሰቶችንና የተድበሰበሱ እውነቶችን ፍለጋ ባደረገው ቅኝትም በርካታ ነገሮች ነቅሶ ያወጣል።
ኦነግ ከኦሮሞ ሕዝብ ሥሪት በተቃረነ መልኩ በአማራ ሕዝብ እና ከየትኛውም ብሔር ኦርቶዶክስ ኾኖ በተገኘ ሁሉ ላይ ያደረሰውን አሰቃቂ ፍጅት ያጋልጣል፤ ያወግዛል::
በኦሮሞ ፖለቲካ ውስጥ የእርጎ ዝንብ የኾኑ እጆችን መንጥሮ ያሳየናል። ፖለቲካኞች እና የፕሮቴስታንት ቸርች ኦርቶዶክሳዊውን ኦሮሞ ከእናት ቤተ ክርስቲያኑ ለመነጠል በቅንጅት የተጫወቱትንና እየተጫወቱት ያለውን ፖለቲኮ ሃይማኖታዊ ቁማር ያስቃኘናል። ለአብነትም የኦሮሚያ ቤተ ክህነትን እንመሠርታለን ብለው ከሚንቀሳቀሱ አካላት ጀርባ ያለውን ሴራ ገላልጦ አስቀምጦልናል።
የአንዲት ሀገር ልጆች እንደመኾናችን ለአብሮነታችን አንዱ ችግር እያንዳንዱ ማኅበረሰብ ራሱን እንዲህ ነኝ ባለው መጠን ዕውቅና ያለመሰጣጣት መኾኑን ያሠምርበታል(ገጽ 13 ፣ 149)::
ጸሐፊው ተግዳሮቶችን፣ ሴራዎችን በመግለጡ ዓላማውን እንዳሳካ ቆጥሮ "ሩጫዬን ጨርሻለሁ" አይልም። ፈተናዎቹን መሻገሪያ፣ ሴራዎቹን ማክሸፊያ መፍትሔዎችን ይጠቁመናል።
የታዩኝ ክፍትቶች :-
👉የዋቢ አጠቃቀስ ቢሻሻል። ለምሳሌ አንዳንድ የሚታወቁ ሐሳቦች ምንጫቸው ሳይጠቀስ ታልፏል፤ አንዳንድ ምንጮች በግርጌ ማስታወሻ ይጠቀሳሉ፤ ሌሎች ደግሞ በዋቢ መጻሕፍት ዝርዝር ውስጥ እንኳ አይገኙም፡፡ ሌላው ደግሞ የአንድን ጸሐፊ ጽሑፍ ሙሉ ለሙሉ ከማካተት ጭምቁን ማካፈል የተሻለ ነው እላለሁ።
👉 የሆሄ አጠቃቀም ላይ ጥንቃቄ ተደርጓል። ነገር ግን አሁንም በጥቂቱ ይቀረዋል፡፡ በሚቀጥለው ኅትመት የቃላት ግድፈት በደንብ ቢታይ ጥሩ ነው::
በመጨረሻ በጸሐፊው አንድ ምክር ዳሰሳውን ልቋጭ ፦" ፖለቲካኞቻችን ለችግራችን ተጠያቂ ማፈላለግ ትታችሁ መፍትሔ ፈልጉልን።"
ዲ. ዮሴፍ ከተማ ሆርዶፋ ሚዛን ለጠበቀ ሥራህ እናመሰግናለን🙏

Comments
Post a Comment